ለሀሰተኛ የማህበራዊ ድረ ገጽ አካውንቶች የህግ ማዕቀፍ ወይስ እገዳ

የዓለም አቀፉ የማህበራዊ ትስስር ድረ ገጽ የሆነው ፌስቡክ ካሉት ከሁለት ቢሊዮን በላይ ተጠቃሚዎች መካከል በሐሰትና በማመሳሰል የተከፈቱት 270 ሚሊዮን መሆኑን ሰሞኑን ባወጣው ሪፖርት አስታውቋል። በኢትዮጵያም የፌስቡክ ተጠቃሚ ከሆኑት አራት ነጥብ አምስት ሚሊዮን ሰዎች መካከል በውሸትና በማስመሰል በባለስልጣናት፥ በታዋቂ ሰዎች እንዲሁም በተቋማት ስም የተከፈቱ አካውንቶች እንዳሉና አሉታዊ ተፅዕኖ እየፈጠሩ መሆኑ ይገለጻል።
የማስመሰል አካውንት ከተከፈተባቸው መካከል ሻለቃ ሃይሌ ገብረስላሴ እንደሚለው፤ እርሱን በማስመሰል በተከፈተው አካውንት ላይ እንደሚተላለፈው መልዕክት ቢሆን ለህይወቱም ጭምር አስጊ ሁኔታ ይፈጠር ነበር። የብዙ ድርጅቶች ባለቤትና ሁለት ሺ ያህል ሰራተኞችን በስሩ የሚያስተዳድር ሲሆን፤ ይህም ጉዳት የእርሱ ብቻ ሳይሆን የበርካቶችም ጭምር መሆኑን ሊታወቅ ይገባል። የውሸት መልዕክት በእርሱ ስም ማስተላለፍም ትልቅ ወንጀል ነው።
ችግሩን ለመፍታት ሲል ወደ ተለያዩ ተቋማት መንቀሳቀሱን የጠቀሰው ሻለቃ ሃይሌ፤ ወደ ፖሊስ ባቀናበት ወቅት ህግ ነውና «የምትጠረጥረው ሰው አለወደ ፍርድ ቤት ሲሄድ ደግሞ «የተጨበጠ ነገር አለመባሉ ጉዳዩን በአጭር ጊዜ ውስጥ ማዘጋት እንዳይችል አድርጎታል። በውሸት ከተነገሩበት መካከል በጣም የረበሸው በተለይ በሶማሌና በኦሮሚያ ክልል መካከል በተከሰተው ሁኔታ ኦሮሚያን ወግኖ እንደቆመ ተደርጎ መነገሩ በሌላው ወገን ሊጠላ የሚያስችለው ከመሆኑም በላይ በህይወቱ ላይም አደጋ ሊያስከትልበት ይችል እንደነበር ነው የተናገረው።
እርሱ እንደሚናገረው፤ እንዲህ አይነቱ ወንጀል በኢትዮጵያ ወንጀለኛ መቅጫ ህግ አልተካተተም። ስለዚህ ራሱን የቻለ ህግ ሊቀረፅ ይገባል። ወንጀሉ ከባድ መሆኑን የሚያውቀው ደግሞ ጉዳቱ የደረሰበት ነው። የበለጸጉ አገሮች አገራቸውንም ሆነ ዜጎቻቸውን የሚከላከሉበት የህግ ማእቀፍ አዘጋጅተዋል።
«እኔ ይህ የውሸት አካውንት እንዲዘጋልኝ ብዙ ዋጋ ከፍያለሁ፤ በጋዜጣም ሆነ በራዲዮ ለማስነገር ገንዘብ አውጥቻለሁ። ብዙ መንገድ ተጉዤም መዝጋት አልተቻለም ነበር። ወደዋናዎቹ ፌስቡክ መስራቾች ዘንድ ሪፖርት በማድረጌና ከፍተኛ ወጪም በማውጣቴ ፍትህ አግኝቼ ሊሆን ይችላል። ይህን ማድረግ የማይችል ግን ህግ ባለበት አገር ማልቀስ የለበትም» ሲል ይናገራል።
ስለዚህ ይህን ጉዳይ መንግስት ሊቆጣጠረው ካልቻለ አገርን የሚያጠፋ በመሆኑ ሊዘጋ ይገባዋል ባይ ነው። ካልሆነ ደግሞ ህግ ሊረቅለት ይገባል ሲል ይገልጻል። በዚህ ፌስቡክ አማካይነት በሚነዛው የውሸት ወሬ የበርካቶች ቤት ፈርሷል፤ የብዙዎቹም ልብ አዝኗል። ከዚህም በላይ አገርን እያሰጋ ያለ ነውና መላ ሊበጅለት ግድ ነው ይላል።
በኢፌዴሪ መንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት የይዘት ማበልጸግና ክትትል ጀነራል ዳይሬክቶሬት ተወካይ አቶ ክፍሌ ወርቁ በበኩላቸው እንደሚናገሩት፤ በማህበራዊ ትስስር ድረ ገጽ ግለሰብም ሆነ ባልስልጣን እንዲሁም ተቋምም የሚያደርገው የመረጃ ልውውጥ ሰፊ የመሆኑን ያህል የመከታተሉ ጉዳይ ከባድ ነው። በህገ መንግስት እንደተደነገገውም ማንኛውም ግለሰብ የራሱን ሐሳብ የመግለጽ መብት አለው።
ይሁንና ይላሉ አቶ ክፍሌ፤ በአገር ላይ አደጋ ያስከትላሉ ተብለው የሚታሰቡትንና በርካታ ተከታይ ያላቸው ከሆኑ ግን ከአገራዊ ፋይዳ በመነሳት ቁጥጥር ይካሄድባቸዋል። በውሸት አካውንት የተከፈተባቸው ግለሰቦችም ሆኑ ተቋማት ግን በስማቸው የተለቀቀው መረጃ የራሳቸው አለመሆኑን ማስተባበል ከእነርሱ ይጠበቃል። አንዳንዱ ግን የእርሱ አለመሆኑን የሚገልጸው ቆይቶ የህዝብን ምላሽ ካየ በኋላ እንደሆነ አስታውሰው፤ ይህ ግን ተገቢ አለመሆኑን ነው ያብራሩት። ከአቅማቸው በላይ ከሆነ ደግሞ ወደ ኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ በማቅናት ስለጉዳዩ መፍትሄ የሚገኝበትን አማራጭ መጠቀም እንደሚቻል ያመለክታሉ።
እርሳቸው እንደሚሉት፤ ዳይሬክቶሬቱ የሚሰራው የተሳሳቱ መረጃዎች ሲገኙ በመያዝ ወደ ህዝብ ትክክለኛው መረጃ እንዲደርስ ለሚመለከታቸው አካላት ማሳወቅ ነው። ነገር ግን በታዋቂ ሰዎችም ሆነ በባለስልጣናት ስም የሚከፈቱ የውሸት አካውንት ላይ ቁጥጥር ወደማድረጉ አይሄድም። ነገር ግን ሚናችን የሚሆነው በአጠቃላይ በማህበራዊ ትስስር ድረ ገጽ ላይ አጀንዳ ሆኖ የቀረበ ጉዳይ ምንድን ነው? ጉዳዩ ለምን ተነሳ? ባለስልጣናትና ግለሰቦች እውን ይህን እያሉ ነው ወይ? ያለውስ ሁኔታ ይህን ያንጸባርቃል፤ አያንጸባርቅም? የሚለውን በማየት የሚመለከታቸው አካላት መልስ እንዲሰጡበት ማድረግ ነው። እነዚህ አካላት ይህ ስህተት ነው አይደለም የሚለውን ይመለከቱታል ማለት ነው። አሊያም ጭራሽ የሌለ ነገር ነው ሊሉ ይችላሉ። ወይም ደግሞ በትክክል ተፈጽሟል ብለው ሊገልጹ ይችላሉ። አንዳንዴ እንዲያውም ከተነገረው በላይ ነው ሊሉም ይችላሉ። በዚህ መልኩ ነው የመረጃ ቅብብሎሹ ውስጥ የምንገኘው ማለት ይቻላል።
አንዳንዴ ማህበራዊ ሚዲያን ለቁጥጥር ሁሉ አስቸጋሪ የሚያደርገው የምንጩ ቶሎ አለመታወቅ ነው። ምንጩ ሁሌ ኢትዮጵያ የሚመስለው አካል አለ። ነገር ግን ከአሜሪካ ወይ ከአውሮፓ ሊሆን ይችላል። ያለው ቴክኖሎጂም ውስብስብ ነው። እንደሚታወቀው በአሁኑ ወቅት ከፌስቡክ አይቻለሁ ብሎ የሚያምን ህዝብ ነው ያለው። ይህን መረጃ ደግሞ ቆም ብሎ ሳያመዛዝን በግርድፉ በመቀበል ወደማስተጋባቱ ደግሞ የሚገባ አካል በርክቷል ይላሉ።
የፖለቲካው ጉዳይ ገኖ ወጣ እንጂ የግለሰቦችን ህይወት የሚፈታተኑ እንዲሁም ትዳር የሚያፈርሱና ሌሎች ማህበራዊ ጉዳይ ላይ ያነጣጠሩ ጉዶች ኢትዮጵያውያኑ ብቻ ሳይሆኑ አውሮፓውያኑም እየታመሱበት ያለ ጉዳይ ነው።
የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ሜጀር ጀነራል ዶክተር ተክለብርሃን ወልደአረጋይ በበኩላቸው፤ ዓለም አቀፋዊ የሆነው ማህበራዊ ድረ ገፅ እያመጣ ያለው የራሱ የሆነ ትሩፋት እንዳለው ሁሉ ችግሮችን ያቀፈ መሆኑ እሙን ነው ይላሉ። ስለዚህም በኢትዮጵያ እየታየ ያለው ችግር ከዓለም አቀፉ ህብረተሰብ ተነጥሎ የሚታይ እንዳልሆነ ነው የሚናገሩት። ፌስ ቡክን ጨምሮ ቲዊተር፤ ዩቲዩብ እና የመሳሰሉት ሁሉ በጎውም መጥፎም ተግባር የሚከናወንባቸው ቢሆንም አሉታዊው ተፅዕኖ እንደየሰውና እንደየአገራቱ መረዳት የሚለያይ መሆኑን ይገልጻሉ።
ዋናው ችግር የሆነው በውሸትም ሆነ በማስመሰል በሚከፈቱም አካውንቶች አማካይነት የሚተላለፉት አሉታዊ መልዕክቶችን ለመቆጣጠር ያስችለው ዘንድ የፌስቡክ ኩባንያ ገና ከጅምሩ ሥርዓቱን ያለመዘርጋቱ ነው። ይህ በመሆኑም በዓለም አቀፍ ደረጃ በሐሰትና በማመሳሰል የተከፈቱት አካውንቶች ያሻቸውን መልዕክት በማስተላለፍ በፖለቲካውም ሆነ በማህበራዊው መስተጋብር ጫና እያሳደሩ ይገኛሉ ይላሉ።
በውሸት በተከፈቱ አካውንቶች የሚተላለፉት መልዕክቶች አገርንም ሆነ የተለያዩ ግለሰቦችን የማጥቆር ዘመቻ ይካሄድበታል። አንዱን ብሄር በሌላው ላይም በክፋት እንዲነሳ የሚያደርጉ ከመሆናቸውም በላይ ባልተገባ መንገድ ህዝብንም ለአመጽ ሊያነሳሱ ይችላል። ይሁንና ድረ ገጹ ለተሻለ ተግባር ሊውል የሚችልና እየዋለም እንደሆነ መታወቁ መዘንጋት እንደሌለበት ሜጀር ጀነራል ዶክተር ተክለብርሃን ይናገራሉ።
እርሳቸው እንደሚሉት፤ ማህበራዊ ድረ ገጽ የራሱ የሆነ አዎንታዊ ገጽታ ስላለው ሙሉ ለሙሉ እንዲቋረጥ ማድረግ አማራጭ ሊሆን አይችልም። ድረ ገጹን ማቋረጥ ማለት አንድ ዜጋ ሐሳቡን የመግለፅ ነፃነት ከማሳጣትም በተጨማሪ ኢኮኖሚ እንዳያድግ እንደመገደብም ያስቆጥራል። ነገር ግን በውሸት እና በማስመሰል የተከፈቱ አካውንቶች በአገርም ሆነ በግለሰቦች ላይ ከሚያደርሱት ቀውስ አኳያ ቁጥጥር ሊደረግባቸውና ሊታገዱ ይገባል።
የችግሩ ሰለባ የሆኑ ግለሰቦችም ሆነ ተቋማት በውሸት የተከፈተው አካውንት የእነርሱ ያለመሆኑን በተቻላቸው ሁሉ በራሳቸው አካውንት ማሳወቁ ይመከራል። ጉዳዩ ጠንከር ያለ ከሆነ ደግሞ ለሚመለከተው አካል ሪፖርት ማድረግ ያሻል። ሪፖርቱ ለራሱ ለፌስ ቡክ መስራችም ሊቀርብ ይችላል። የሚተላለፈው መልዕክት አገራዊ ደህንነትን የተመለከተ ከሆነ ለኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ (ኢንሳ) ሪፖርት ማድረግ ይቻላል።
በማህበራዊ ድረ ገፅ ላይ በሚተላለፉ ያልተገቡና የጥላቻ መልዕክቶች ምክንያት በኢትዮጵያም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ ጫና መፈጠሩ ይታወቃል። በአገር አቀፍ ደረጃ በቅርብ ከተፈጠረው ክስተት መካከል አምና በተከበረው በኢሬቻ በዓል ላይ የተገኘውን የበዓሉ ታዳሚ የአየር ሃይል ሂሊኮፕተር መደብደቡ በስፋት መነገሩ ይታወሳል። በኦሮሚያና ሶማሌ ክልሎች መካከል የተፈጠረውን ያለመግባባት ምክንያት በማድረግ ችግሩ የበለጠ እንዲጋጋል ዘመቻ ሲካሄድ ቆይቷል። በዓለም አቀፍ ደረጃም ሊቢያ፤ ሶሪያ፤ የመንም የየራሳቸው ችግር ቢኖርባቸውም ማህበራዊ ድረ ገጹም ላጋጠማቸው ቀውስ የራሱን ሚና ተጫውቷል።
ዋና ዳይሬክተር ሜጀር ጀነራል ዶክተር ተክለብርሃንም ሆኑ አቶ ክፍሌ እንደሚሉት፤ ለዚህ መፍትሄው ራሱን የቻለ ፖሊሲ በአገር አቀፍም ሆነ በአህጉር ደረጃ መቅረፅ ያሻል። ይሁንና ህግ ማውጣት ብቻ በራሱ በቂ ስለማይሆን በዘርፉ ያለውን ባለሙያ አቅም መገንባትም ግድ ይላል። ከዚህ በተጨማሪ የተጠቃሚው ንቃተ ህሊና ሊጎለብትና የሚነገሩ ነገሮችን እውነትነት ሙሉ ለሙሉ ከመቀበሉ በፊት ሊጠይቅና ሊያገናዝብ ያስፈልጋል። ይህ ካልሆነ የማህበራዊ ትስስር ድረ ገጾች የጠቀሜታቸውን ያህል አፍራሽ ሚና መጫወታቸውን ይቀጥላሉ።

Comments

Popular posts from this blog